ባንካችን ቃል በገባው መሠረት 2 ዘመናዊ መኪኖችን ለዕድለኞች አስረከበ

ባንካችን ቃል በገባው መሠረት 2 ዘመናዊ መኪኖችን ለዕድለኞች አስረከበ

ባንካችን አቢሲንያ በቅርቡ ባካሄዳቸው ሁለት የሽያጭ ዘመቻዎች የዘመናዊ መኪና ሽልማት አሸናፊ ለነበሩ ሁለት ደንበኞች ዛሬ ግንቦት 13 ቀን 2018 ዓ.ም በዋናው መ/ቤት በተካሄደ ደማቅ ሥነ-ሥርዓት ሽልማታቸውን አስረከበ። 

በዚህም መሠረት ለሁለተኛ ጊዜ በተካሄደው “ከአቢሲንያ ባንክ ጋር ይጀምሩ – ያድሱ እና ይደጉ”የሽልማት መርሐ-ግብር አሸናፊ ለሆኑት የባንካችን የፍልውሃ ቅርንጫፍ ደንበኛና በከተማችን በአንድ የግል የህክምና ክሊኒክ ሐኪም ለሆኑት ዶ/ር ዮሴፍ ገ/መድህን ሃዩንዳይ አክሰንት ሴዳን መኪና አስረክቧል። 

እንዲሁም ማርች 8ን በማስመልከት ለ5ኛ ጊዜ በተካሄደው የ“እችላለሁ!” መርሐ-ግብር ዕድለኛ ለሆነችው የባንካችን ጅማ ዲስትሪክት ሄርማታ ቅርንጫፍ ደንበኛ ዶ/ር ቤተልሄም ይትባረክ የ2025 ቢ.ዋይ.ዲ ሴጉል መኪና ሽልማት ሰጥቷል። 

በዚህ የሁለቱ የሽያጭ ዘመቻዎች ይፋዊ መዝጊያና የሽልማት ሥነ-ሥርዓት ላይ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት  የባንካችን ቺፍ ኤንተርፕራይዝ ሰርቪስ ኦፊሰር  ወ/ሮ መሠረት አስፋው ዕድለኞቹን “እንኳን ደስ ያላችሁ!” ካሉ በኋላ ከሌሎች የባንካችን ከፍተኛ የሥራ አመራር አባላት ጋር በጋራ በመሆን ሽልማቱን አስረክበዋል። 

ወ/ሮ መሠረት የ “ይጀምሩ፣ ያድሱ እና ይደጉ” መርሐ-ግብር አዳዲስ ደንበኞች ከባንካችን ጋር እንዲሰሩ፣ ነባሮቹ ግንኙነታቸውን እንዲያድሱ እንዲሁም ሁሉም ደንበኞች ከባንካችን ጋር አብረው እንዲያድጉ ለማበረታታት የተካሄደ ሲሆን፣ የ“እችላለሁ!” መርሐ-ግብር ደግሞ ባንካችን የሴቶችን የፋይናንስ አቅም ለመገንባት ያለውን ቁርጠኝነት ለማሳየት ያለመ እንደነበር ገልጸዋል። በሁለቱም  መርሐ ግብሮች የተለያዩ የማበረታቻ ሽልማቶች እንደተካተቱም ጨምረው ገልጸዋል።

በዚህ ደማቅ የሽልማት ሥነ-ሥርዓት ላይ የባንካችን ከፍተኛ የሥራ አመራር አባላት፣ የኢትዮጵያ ደም እና ሕብረ-ሕዋስ አገልግሎት አመራሮች፣ የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት ተወካዮች፣ የሚዲያ አካላት እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Call Now Button